Tuesday, March 17, 2015

ቤተ-ክርስቲያን የማን ቤት ናት ? የማን ቤት ናት ? የማን ቤት ናት ? በላስ ቬጋስ ከተማ የምንኖር ህዝበ-ክርስቲያን ፤ በቅርቡ በቤተ-ክርስቲያናችን በደብረ ምህረት ቅዱስ ሚካኤል ካህናትና በሰበካ ጉባኤው ላይ በተደረገ ምርጫ ምክንያት ችግር ተፈጥሮ ነበር ። ችግሩን በመመካከር ለመፍታት ከመሞከር ይልቅ ለአመታት ካገለገሉበት ቤተ-ክርስቲያን የአሪዞና የዩህታና የኔቫዳ ሊቀ-ጳጳስን አቡነ ዮሴፍንና ካህናቱን ከስራ የሚያሰናብት ደብዳቤ ተልኮላቸው በቅርቡ ወደተገዛው ቤተ-ክርስቲያን ድርሽ እንዳይሉ ይነገራቸዋል ። ጉዳዩ እስከ ፖሊስ ድርሶ እስካሁን መፍትሄ ያላገኘ ጉዳይ ሆኗል ። እኔ ዛሬ ይህን መልእክት እንድፅፍ ያነሳሳኝ ማን በደለ ማን ተበደለ ለማለት አይደለም ። ምንንም ለመወንጀልም ሆነ ለመኮነን ፍላጎትም የለኝም ። ጳጳሱን አቡነ ዮሴፍን ጨምሮ ካህናቱ ወደቤተ ክርስቲያኒቱ እንዳይደርሱ ህጋዊ ደብዳቤ ከደረሳቸው በኋላ ፤ ለጊዜውም ቢሆን ምእመናኑን ለመሰብሰቢያ ተከራይተውት ከነበረው ቤተ- ክርስቲያን ድረስ ተሂዶ በሲኖዶስ የተወገዙ ናቸው አታከራዩአቸው በሚል ካህናቱ ቦታ አጥተው ምእመናኑን ባለፈው ሳምንት እሁድ በፓርክ ሰብስበውት ፀሎት ተደርጎ ተበትኖ ነበር ። በዚሁ እለት በፓርኩ የተገኘው ህዝበ- ክርስቲያን በሰርቢያ ኦርቶዶክስ ቤተ-ክርስቲያን የመምለኪያ ቦታ የሚያገኝበትን መንገድ ለመሻት ረቡዕ ፊብሩዋሪ 25 ቀን ቀጠሮ ይዞ ተለያዬ ። በቀጠሮው ቀን የተገናኙት ካህናትና ህዝቡ በዬራሳቸው ዝግጅት አድርገው ነበር የመጡት ። በእለቱ በብፁዕ አቡነ ዮሴፍ ግብዣ የዲሲና ሜሪላንድና ሊቀጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል ሳይታሰብ በቦታው መገኘት በህዝበ ክርስቲያኑ ላይ ተጨማሪ የደስታ ድባብ ዘረጋበት ። በመምህር ውብ አምላክ አስተናጋጅነት የተከፈተው የቀጠሮ ጉባኤ በብፁዕ አባታችን በአቡነ ሳሙኤል ፀሎት ከተከፈተ በኋላ የደብረ- ብስራት ቅዱስ ገብርኤል ታቦት በሚቀጥለው ቀን እንደሚገባ ሲበሰር ወይዛዝርቱ በእልልታ ወንዱ በጭብጨባ መዘምራን በምስጋና መዝሙር አዳራሹን ሞሉት ። ይህን ብስራት የናኙልን ደግሞ የእለቱን ትምህርት “ቤተ-ክርስቲያን የማን ናት ?”†በሚል ርእስ የጀመሩት ድምፀ- ነጎድጓዱ ሊቀ-ህሩያን ቀሲስ መላኩ ባወቅ ነበሩ ። በትምህርታቸው ላይ የዚህች ቤተክርስቲያን አባልነታችሁ በአባልነት ፎርም ሳይሆን በጥምቀታችሁ ነው ሲሉ ህዝቡ በእኩልነትና በአንድነት መንፈስ የኢትዮጵያ ድርቶዶክስ ቤተ-ክርስቲያን አባልነቱን አረጋገጡለት ። ክርስቲያኖች በተሰበሰቡበት ሁሉ የእግዚአብሂር መንፈስ ይኖራልና ፤ እዚህ ቤተ-ክርስቲያን እንዳትደርሱ የተባሉት ካህናት ህዝቡ በሰጣቸው ፍቅርና ሙቀት ፤ ባሳየቸው አንድነት ፊታቸው በደስታ ጸዳል ሲሞላና ስብራታቸው ሲጠገን እዚያው የነበርን ሁሉ ምስክሮች ሆንን ። ንብ ያለአውራው ባዶ እንደሆነ ሁሉ ፤ ህዝበ-ክርስቲያንም ያለ ካህናት ባዶ ነው ። ንብ በአውራው አማካይነት የመንጋውን ዘር ቋሚ የህይወት ቀጣይነት እንደሚያረጋግጥ ሁሉ ካህናትም የምእመናኑን መንፈሳዊ ህይወት ጠባቂዎች ናቸው ። በዚህ ወከባና ጩሀቱ በበዛበት አለም ካህናት የእግዚአብሄር እንደራሴዎች ናቸው ። እነዚህን የመንፈስ አባቶች ነው በሥጋዊው ህግ በብጥሽ ወረቀት ወደቤተ-ክርስቲያኒቱ እንዳይደርሱ የተወሰነባቸው ። የአምልኮት ተግባራችንን መፈፀም የሚያስችለን ካህናቱ ስርዓተ-ቅዳሴውን ሲመሩት ብቻ ነው ያለው ህዝበ-ክርስቲያን አውራዎቹን ይዞ በማምለኪያ ቦታ እጦት ለሳምንታት ተንከራተተ ። ብርድና ነፋሱ ሳያግዱት ምእመኑ ህጻናት ልጆቹን ይዞ በህዝባዊ ፓርክ ውስጥ የአንድ ሰንበት አምልኮ አደረገ ። ከላይ የጠቀስኳት የቀጠሮዋ ቀን ፌብሯሪ 25 በላስ ቬጋስ ኔቫዳ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳዊ ተዋህዶ ክርስትያናዊ ታሪክ ታላቅ ቀን ሆና የምትታሰብ ናት ። ምሽት ላይ በሰርቢያ ኦርቶዶክስ ቤተ- ክርስቲያን አዳራሽ የተሰበሰበው ህዝብ ለላስ ቬጋስ አዲስ የሆነውን የደብረ-ብስራት ቅዱስ ገብርኤል ታቦት በማግስቱ እንደሚገባ ብስራቱን ሲሰማ ፤ ታቦታችንማ በድህነት አይገባም ሲል ሁለት ሰአት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ $104 ሽህ 845 የአሜሪካን ዶላር በማዋጣት አከበረው ። ወንዱ የጣቱን የወርቅ ቀለበት ሴቷ የአንገቷን ሃብል እያወለቀች የታቦቱን ግባት ቀን በደስታ አከበርነው ። በማግስቱም ታቦቱ ሲገባ የዋዜማው በረከት ያልደረሳቸው ወንድሞችና እህቶች እኛስ ለምን ይቀርብናል በረከቱ ለኛም ለቤታችንም ይትረፍ በማለት ተጨማሪ $23 ሺህ በማዋጣት አዲሱን ታቦት ተቀበሉት ። ብፁእ ወቅዱስ አቡነ ዮሴፍ ካደረጓቸው ንግግሮች ውስጥ አንድ የሩሲያ ሰው የትናገረው ነው በማለት እንዲህ ያሉት ይጠቀሳል ። “ሰው ገፍቶ ገፍቶ ከክርስቶስ እግር ስር ጣለኝ”†አዎ ይህን የተናገረው የሩሲያ ታዋቂ ደራሲ ደስተዮቭስኪ ነበር ። ደስቶዮቭስኪ በድርሰት ስራዎቹ ምክንያት ብዙ መከራ ደርሶበታል ። ከዚያም ፍርድ ቤት ቀርቦ የሞት ፍርድ ተፈርዶበታል ። የፍርድ ቀኑ ደረሰችና የሞት ቅጣቱን ፈፃሚዎቹ የመስቀያውን ገመድ አንገቱ ውስጥ አስገቧት ። ሸምቀቆው እየጠበቀ እየጠበቀ ትንፋሹ እያጠረች ስትሄድ ለመጀመሪያ ጊዜ የክርስቶስን ስም ጠርቶ እንዲያድነው ተማፀነ ። ወዲያው የመሰቀያው ክፍል በር ተከፈተና የሩሲያው ንጉስ መልክተኛ ፈጥኖ ገባ ። ከንጉሱ የተጻፈውንም መልእክት ከፍ አድርጎ አነበበው ። የሞት ቅጣቱ ተሽሮ በሩሲያው ንጉስ ምህረት ተደርጎልሃል የሚል ነበር ። ምሳሌው ለሁላችንም ግልፅ ነው ብዬ እገምታለሁ ። ህዝብ ያቀፈው ህዝብ የወደደው ዘለአለማዊ ነው ። በላስ ቬጋስ ላለፉት አስራ አራት አመታት የክህነት ተግባራቸውን ሲያከናውኑ የነበሩት መልአከ-ብስራት ቆሞስ አባ ወልደየሱስም በተፈጠረው ሁኔታ ምክንያት ጨልሞ የነበረው ፈገግታቸው በምእመናኑ ፍቅርና ሙቀት እንደተመለሰላቸው ሊቀ-ሕሩያን ቀሲስ መላኩ ባወቅ ሲናገሩ ህዝቡ በእልልታ አዳራሹን ሞላው ። በመጨረሻም የብፁዕ ውቅዱስ አቡነ ዮሴፍን መልእክት እንዲህ ይላል ። የአገረ-ስብከቴ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቤተሰቦች ፤ ይህ ያከበራችሁት የደብረ ብስራት ቅዱስ ገብረኤል ታቦት የገባባት ቤተ-ክርስቲያን አባልነት በጥምቀታችሁ ብቻ ነው ። በተለያዩ ምክያቶች የአባልነት ክፍያ መክፈል ቢያቅታችሁ እንኳ በጥምቀት የክርስቶስ ልጆች ናችሁና አባልነት የሚከለክላችሁ የለም ። የአባልነት መታወቂያ ይኖራችኋል ። ዋናው በሃይማኖታችሁ መፅናት ነው ። ክርስቲያናዊ ፍቅራችሁና አንድነታችሁን እንዲሁም ፅናታችሁን ይህ ክፉ ቀን አሳይቶናልና አሁን እንዳላችሁት ሁሉ ሳትለያዩ ተፋቅራችሁ ተከባብራችሁ ኑሩ ። እኛ ለሚበድሉን ሁሉ እንፀልያለን ። ይህ ክርስትያናዊ የተሰጠን ግዴታችን ነው ። ከተለዩን ጋርም በአምላካችን ፈቃድ አንድ እንደምንሆን ተስፋየ ነው ብለዋል ። ከዚያም ይህች ቤተ-ክርስቲያን የምትተዳደረውም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሪዎስ ርዕሳነ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ስር ባለው ሲኖዶስ መሆኑንም ገለፀዋል ። እንግዲህ ቤተ-ክርስቲያን የማናት ? የእግዚአብሄር ቤት ናት ። የናንተ ቤት ናት ፤ እናንተ በእምነታችሁ በተሰበሰባችሁበት ቤት ሁሉ የእግዚአብሄር መንፈስ አለ ፤ ካሉ በኋላ በዚህ በክፉ ቀን ሊያፅናኑን ከዋሽንግቶን ዲሲ ድረስ የመጡትን የዋሽንግተንና የሜሪላንድ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤልን ፤ ከኔው ጋር መገፋቱ የደረሰባቸውን መላከ ብስራት ቆሞስ አባ ወልደየሱስን ፤ ከካሊፎርኒያ ድረስ ሊያበረታቱን የመጡትን ሊቀህሩያን ቀሲስ መላኩ ባወቅን ፤ ከኛ ቀድሞ የተገፋውን መምህር ውብ አምላክን ፤ ሁሌም ካጠገባችን ሳይለዩ አብረውን የቆሙትን ሊቀ- ጠበብት ዳኜ ፈረደን ፤ እኛማ ከአባቶቻችን አንለይም ሲሉ አብረውን የተንከራተቱትን ዲያቆናቱን በመጨረሻም ብርዱም ነፋሱም መንከራተቱም ሳያሸንፋችሁ አብራችሁኝ ለቆማችሁት ልጆቼ ፤ ከቅርብም ከሩቅም በስልክም ሆነ በኢሜል የማፅናኛ መልእክታችሁን ለላካችሁልን ሁሉ የእግዚአብሄር በረከት ቤተችሁን ይሙላ ፤ የኔም ምስጋና ይድረሳችሁ ፤ በፀሎቴም ሁሌ አስባችኋለሁ ፤ ብለዋል ። ከብስራተ-ገብርኤል ፡ ማርች 1 ቀን 2015 ። 

No comments:

Post a Comment